Thursday, June 2, 2016

#OromoProtests

ለክቡር አቶ ሽፈራው ሽጉጤ፣ የትምህርት ሚኒስቴር ሚኒስትር
ጉዳዩ: የከፍተኛ ትምህርት ተቋማት መግቢያ ፈተና (EUEE) በተመለከተ ፍትሃዊ የሆነ የመርሃግብር ምክረ ሃሳብ (program proposal) ስለማቅረብ ይመለከታል።
የተሰረዘውን ፈተና በተመለከተ መስሪያ ቤትዎ ያወጣውን መርሀ ግብር ተመልክተነዋል። ሆኖም ግን መርሃግብሩ ከታች በተገለጹት ምክኒያቶች ሊሻሻል ይገባዋል ብለን ስለምናምን የሚከትለውን ምክረ-ሀሳብ ልናቀርብ እንወዳለን። በደንብ ሊጤን የሚገባው ነጥብ ይህንን ምክረ-ሀሳብ በማጥናቀር ሂደት ውስጥ ከ5000 በላይ ተማሪዎች በግልጽ በሶሻል ሚዲያ ሀሰባቸውን ሰጥውበታል። 123 መምህራንን ከሁሉም የኦሮሚያ ዞኖች በቀጥታ አማክረናል። ተማሪዎቹም ሆኑ መምህራን በዋናው ጉዳይ ተመሳሳይ አቋም አንጸባርቀዋል። የተማሪዎቹም ሆነ የመምህራኑ ሀሳብ የሚያመለክተው በመስሪያ ቤትዎ ለድጋሚ ፈተናው የተሰጠው የአንድ ወር ጊዜ በቂ አለመሆኑንና ጊዜውን ማራዘሙ ግዴታ ነው የሚል ነው። አብዛኛዎቹ የኦሮሚያ ተማሪዎች (80%) ያመለጥንን የ6 ወራት ትምህርት ለማካካስ እና ለፈተናው ለመዘጋጀት ቢያንስ 12 ሳምንታት ወይም 3 ወራት ያስፈልግናል ብለዋል።
እንደአዲስ የወጣው የፈተና መርሀ ግብር ከጊዜ ማጠር በተጨማሪም ሌላ ግድፈት እንደለው ከተማሪዎች እና መምህራኖች ጋር ባደርግነው ምክክር ተገንዝበናል። ይሄውም መርሃግብሩ በረሞዳን ጾም ወር መጨረሻ ላይ መሆኑ በሁለት ዋና ዋና ምክንያቶች ትክክል አንዳልሆነ ተረድተና።
1) ሳይንሱም እንደሚያረጋግጠው የሰው ጭንቅላት (brain) በፈተና ጊዜ በደንብ ለማሰብ ከፍተኛ የምግብ ሃይል አቅርቦት (high energy supply) ይጠቀማል። የጾም ወቅት ደግሞ የጿሚዎቹ ጭንቅላት ባንጻራዊ መልኩ ሃይል-አጠር (hypo) ስለሚሆን ጿሚ ተማሪዎችን በእንደዚህ ዓይነት ወቅቶች ለዛውም ሙሉ ቀን ረጃጅም ፈተናዎች ላይ እንዲቀመጡ ማድረግ አይመከርም። በተለይ ደግሞ ጉዳዩ ሃይማኖታዊ ሆኖ የሚጾሙና የማይጾሙ ተማሪዎች የሚወስዷቸውን ፈተናዎች በእንደዚህ ዓይነት ወቅቶች መስጠት ትክክል አይደለም ። ግልጽ የሆነ መድሎ (clear discrimination) የማድረግ ያህልም ሊቆጠር የሚችል፤ ማህበራዊ መተሳሰብን ብሎም ህገ-መንግስቱን የሚጥስ ነው።
2) በድጋሚ ባወጠችሁት መግለጫም ፈተናው የኢድ አልፈጥርን ቀን እንደሚዘል ገልጻችኋል። ይህ ማለት በኢድ ዋዜማ እና በማግስቱ ፈተና ይኖራል ማለት ነው። በማህበረሰባችን የበዓላት ሰሞን በግርግርና ለፈተና ትኩረት ፍጹም በማይመቹ (exam mood eroding) ማህበራዊና ቤተሰባዊ መስተጋብሮችና ፌሽታዎች የተሞላ መሆኑን ሁላችንም የምናውቀው ሃቅ ነው። ይህ ደግሞ ተረጋግቶ ለማጥናት የሚያስቸግር ከባባዊ ሁኔታ (distractive environment) በመፍጠር ተማሪዎች ለፈተናው ሙሉ ትኩረት እንዳይሰጡ ያደርጋቸዋል። እናም ፈተናን በእንደዚህ ዓይነት ትልቅ ዓመት በዓል ወቅት ማድረግ ለሃይማኖቱ ተከታይ ተማሪዎች ከፍተኛ ጉዳት እንደሚኖረው ግልጽ ግልፅ ነው።
የምናቀርበው ምክረ-ሃሳብ በተማሪዎቹ ምቾትና አስተያየት ላይ ብቻ በመመርኮዝ እንዳይሆን ሌሎች ባለ ድርሻዎችንም አማክረናል። አዲሱ ፈተና ተዘጋጅቶ፣ ታርሞ ውጤቱ እስኪታወቅ ድረስ ያለውን ሂደት ከግንዛቤ በማስገባት፣ ከዚህ በፊትና አሁንም በትምህርት ሚኒስቴር ውስጥ በፈተና ጉዳዮች ላይ የሰሩ ባለሟያዎችን አማክረናል። እንዲሁም ፈተናው የዩኒቨርሲቲዎችን የሚቀጥለውን አመት መርሀግብር ሊያውክ ስለሚችል ፕረዚደንቶችን ጨምሮ የተለያዩ የዩኒቨርሲቲ መምህራንና የአስተዳደር ዘርፍ ሰራተኞችን አማክረናል።
ስለሆነም ከዚህ በላይ ከገለጽናቸው ምክኒያቶችና ባሰባሰብናችው ሙያዊ አስተያየቶች ላይ ተመርኩዘን ከዚህ ቀጥሎ የተዘረዘሩትን የመረሃግብር ምክረ ሃሳቦችን እናቀርባለን። ለተፈጻሚነታቸውም ከእርሶ መስሪያ ቤት በኩል በጎ ምላሽ እንደሚኖር ተስፋ እናደርጋለን:
1) ለተማሪዎቹ ሁለት ወር ቢሰጣቸው እና ፈተናው ከሃምሌ 25 እስከ 28 ወይም ከዚህ ጊዜ በኋላ በሚመቻቹ ወቅት ቢሆን ፍትሃዊ ይሆናል።
2) ባሉት ሁለት ወራት ውስጥ ተማሪዎች በቂ ዝግጅት እንዲያደርጉ ከዚህ ቀደም ያስረከቧቸው መጽሃፍትና ሌሎች የጥናት መርጃ መሳሪያዎች ቢመለስላቸው ጥሩ ይሆናል።
3) በተለይም በኦሮሚያ ተማሪዎች ላልተማሯቸው ክፍለጊዜዎች መምህራኑ ማካካሻ (make up classes) እንዲሰጧቸው ማድረግ ያስፈልጋል። ክረምቱ የእረፍት ጊዜያቸው መሆኑን ከግንዛቤ በማስገባት ለመምህራኑ ማበረታቻ (incentives) የሚደረግበት መንገድ ቢዘጋጅ።
4) ጊዜው የዩኒቨርሲቲ ተማሪዎች ለእረፍት ወደ ቤታቸው የሚመለሱበት በመሆኑ እነዚ ተማሪዎችም የየኣካባቢዎቻቸውን ተፈታኝ ተማሪዎች በቱቶር ማስጠናት ወይም በሌሎች መንገዶች ለፈተናው ዝግጅት ይረዷቸው ዘንድ የማበረታቻ መንገዶች ቢመቻቹ።
5) ለክረምቱ ወደየትውልድ ቦታቸው የሚመልሱ የዩኒቨርሲቲ ተማሪዎች ለተፈታኞቹ የማስጠናት (tutorial) ድጋፍ እንዲሰጡ ትምህርት ቤቶች እና የአስተዳደር ክፍሎች ሁኔታዎችን እንዲያመቻቹ ማድረግ።
6 ) በተለይም በኦሮሚያ አካባቢ በፖሊስና በመከላከያ ሃይሎች በተማሪዎች ላይ የሚደረገው ወከባና ተጽዕኖ እንዲቆም፣ እነዚ የታጠቁ አካላት ከትምህርት ቤቶች አካባቢ እንዲርቁ፣ የታሰሩ ተማሪዎችም ተለቀው ከላይ በተጠለተው መልኩ ለፈተናው ዝግጅት እንዲጀምሩ ቢደረግ።
በመጨረሻም፣ ከዚህ በፊት የወሰድናቸው እርምጃዎችም ሆኑ አሁን ያቀረብነው ምክረሃሳብ መነሻነቱ ፍትሃዊነት፣ የእኩል እድል ተጠቃሚነት እንዲሁም የተወዳዳሪነት መርህን የተከተለ የፈተና ስርዓት በሃገሪቱ እንዲረጋገጥ ማድረግ እንደሆነም ደግመን መግለጽ እንወዳለን። ለዚህም ከኛ በኩል ያለውን መልካም ፈቃድ (good faith) ይበልጥ ለማረጋገጥ በእጃችን ያሉትን ሌሎቹን የፈተና ቡክሌቶች ሚስጥራዊነት እንደምንጥብቅና አዲስ ለምታዘጋጁት ፈተናዎች ሚስጥራዊነት መጠበቅም የበኩላችንን አስተዋጽዕ እንደምናደርግ ቃል እንገባለን። ያቀረብነውን ምክረሀሰብ በሚገባ አጢናችሁ በበኩላችሁም ጉዳዩ የሚመለከታቸውን ባለጉዳዮች አማክራችሁ ፍትሃዊ ውሳኔ ላይ እንደምትደርሱ ተስፋ እናደርጋለን። ነገር ግን አሁን ያቀረብነው ምክረሀሳብ ወደጎን ተትቶ፣ እንደክዚህ በፊቱ የኦሮሚያ ተማሪዎች እሮሮ ጆሮ ዳባ ልበስ ተብሎ ፍርደገምድል በሆነ መልኩ አሁን የተቀመጠውን የፈተና መርሃ ግብር ወደ ማስፈጸም የምትሄዱ ከሆነ በእርግጥኝነት ለሚደርሰው ዳግም ሀገርዊ ኪሳራ ተጠያቂነቱ የትምህርት ሚኒስቴር መሆኑን ከወዲሁ ልናስጠነቅቅ እንወዳለን።
ከሰላምታ ጋር!
‪#‎OromoProtests‬
ግልባጭ፡
-ለኢፌድሪ ፕረዚደንት ጽ/ቤት
- ለኢፌድሪ ጠቅላይ ሚኒስትሩ ጽ/ቤት
- ለኢፌድሪ ህዝብ ተወካዮች ምክር ቤት አፈጉባኤ ጽ/ቤት
- ለኦሮሚያ ብሄራዊ ክልላዊ መንግስት ፕረዚደንት ጽ/ቤት
- ለጨፌ ኦሮሚያ አፈ ጉባኤ ጽ/ቤት
- ለሁሉም ክልሎች ትምህርት ቢሮዎች
- ለመላው የኢትዮጲያ ህዝብ
-ለሁሉም የ 12ኛ ክፍል ተፈጣኝ ተማሪዎች
- ለሁሉም ኢትዮጵያ ተኮር ሚዲያዎች

No comments: